“በዴሞክራሲ ውስጥ የሚነሱ ጥያቄዎች በአንድ ጀምበር የሚቋጩ ሳይሆን ጊዜ የሚጠይቁ ናቸው”- አቶ ሌንጮ ለታ

“በዴሞክራሲ ውስጥ የሚነሱ ጥያቄዎች በአንድ ጀምበር የሚቋጩ ሳይሆን ጊዜ የሚጠይቁ ናቸው”- አቶ ሌንጮ ለታ

በዴሞክራሲ ውስጥ የሚነሱ ጥያቄዎች በአንድ ጀምበር የሚቋጩ ሳይሆን ጊዜ የሚጠይቁ መሆናቸውን የቀድሞ የኦሮሞ ዴሞክራሲያዊ ግንባር ሊቀመንበር አቶ ሌንጮ ለታ አስታወቁ ። ሁሉን በእኩል የሚያይ ህገ መንግሥትና ሁሉንም የምትመስል ኢትዮጵያ ፈጥረን ቢሆን ኖሮ የብሔተርኝነት አባዜ አይኖርም ነበር ሲሉም አመለከቱ።

አቶ ሌንጮ በተለይ ከአዲስ ዘመን ጋዜጣ ጋር ባደረጉት ቃለ ምልልስ እንዳስታወቁት፣ በዴሞክራሲ ውስጥ የሚነሱ ጥያቄዎች ጊዜ የሚፈልጉ ናቸው። በተለይ ብዝሃነትን በአግባቡ በማስተናገድ ጥያቄዎችን ለመመለስ የሚደረገው ጥረት በአንድ ጀምበር የሚቋጩ አይደለም ።እንግሊዝ የዴሞክራሲ ተሞክሮዋ የዳበረ እንደሆነ ያመለከቱት አቶ ሌንጮ ፣ ነገር ግን ዛሬም የስኮትላንድ፣የዌልስና የምዕራብ አየርላንድ ጥያቄ አለባት ። ይህንን አጣጥመው የተሻለ ፌዴራል ስርዓት ለመፍጠር እየሰሩ ይገኛሉ ብለዋል።

በሌላ በኩል የአንድ ብሔር የመንግሥት ስርዓት በአውሮፓ ለማስፋፋት ከፍተኛ ጥረት ስታደርግ የነበረችው ፈረንሳይ ፣ ዛሬ የአንድ ብሔር ሀሳብ ስላልተሳካ በፈረንሳይ ኮርሲካ ፌዴራል ስርዓትን ተቀላቅላለች ያም ሆኖ ግን እዚያም ጥያቄዎች እንዳሉ አመልክተዋል።በተመሳሳይ መልኩ ጎረቤታችን ሱማሊያን ብንወስድ አንድ ብሔር፣ አንድ ሀይማኖትና አንድ ባህል በመኖራቸው ከግጭቶች፣ከአለመግባባቶችና ሌሎች ማህበራዊና ፖለቲካዊ ቀውሶች ሊተርፉ እንዳልቻሉም አስታውቀዋል ።በአገራችንም የሚስተዋሉ ችግሮች በለውጡ ምክንያት ተገፍተው የወጡና ህዝቡ ከአፈና ስርዓት ከመላቀቁ ጋር የተያያዙ መሆናቸውን መገንዘብ ያስፈልጋል ያሉት አቶ ሌንጮ ፣ አንዳንድ ብሔሮች ያገኙት አንጻራዊ መብት ልንቀማ እንችላለን ብለው ጥርጣሬ ውስጥ በመሆን ሲወራጩ ግጭቶች ሊፈጠሩ እንደሚችሉም ጠቁመዋል ።

ችግሮቹን እንደ መልካም አጋጣም በመጠቀም ወደ መልካም መለወጥ እንጂ የዓለም ክስተት እንዳልሆነ አድርጎ መነታረክ ተገቢ እንዳልሆነ ጠቁመው ፣የሚነሱ ጥያቄዎች ከኋላቀርነት የሚመነጭ ሳይሆን የዓለም ተሞክሮ ውጤትም ጭምር ናቸው ብለዋል ።ኢትዮጵያ ህዝብ በአመዛኙ አንድነቱን ይፈልጋል። የቀደሙት አባቶችም ቢሆን ለአገሪቱ አንድነት ብዙ ለፍተዋል ግን ደግሞ ሲወገዙ እንሰማለን። የአሁን አንድነት የአክራሪ ብሔርተኞች መፈንጫ ነው የሚሉ ወገኖች አሉ። እርስዎስ በዚህ ላይ ምን ይላሉ ተብለው የተጠየቁት አቶ ሌንጮ፤

“እኔ ለኢትዮጵያ አንድነት ላለፉት ሁሉ ክብር አለኝ። ሆኖም በጉልበት አንድ ለማድረግ የተሞከረው ነገር ስህተት ነበር ። በመፈቃቀድ ላይ የተመሰረተ አንድነት ቢሆን ኖሮ የት በደረስን ነበር። ብሔርተኝነትም ቢሆን የሚያቆጠቁጠው በአንድነት ውስጥ ኮታና ቦታ ሲጠፋ ነው። ሁሉን በእኩል የሚያይ ህገ መንግሥትና ሁሉንም የምትመስል ኢትዮጵያ ቢኖረን እርግጠኛ ነኝ የብሔተርኝነት አባዜ ያከትማል” የሚል ምላሽ ሰጥተዋል። “ለእኔ ኦሮሞነትን ይዤ ወደ ኢትዮጵያዊነት እንድገባ ከተፈቀደልኝ ያለምንም ማቅማማት እቀበላለሁ” ያሉት አቶ ሌንጮ ፤ አክራሪ ብሔርተኛ መሆን ግን አደጋ ስላለው መሆን አልፈልግም” ብለዋል። በኢትዮጵያ ስም ማንነትን ከሌላ በተለየ መልኩ ማጎላትም ራሱ አክራሪ ብሔርተኝነት ስለሆነ መጠንቀቅ እንደሚያስፈልግ በአሳስበዋል።

በአጠቃላይ ማንነትን ይዘው ኢትዮጵያን መቀላቀል ለአገሪቱ ጥቅም እንጂ ቅንጣት ጉዳት እንደሌለው አስገንዝበዋል ።አዲስ ዘመን ጥር 18/2013

Share this post