በር ያስገባል በር ያስወጣል፤ ወዴት ያስገባል ወዴት ያስወጣል

በር ያስገባል በር ያስወጣል፤      ወዴት ያስገባል ወዴት ያስወጣል

በር መሸጋገሪያ ነው፤ ከአዲስ ወደ አሮጌ መሻገሪያ፤ ከአሮጌ ወደ አዲስ መሻገሪያ። ከሞት ወደ ሕይወት። ከሠፈር ወደ ሌላ ሠፈር። ከዛሬ ወደ ነገ። ከሹመት ወደ ሽረት፤ ከሽረት ወደ ሹመት። ሽግግሩ አንዳንዴ በምርጫ ነው፣ አንዳንዴ ያለምርጫ። መወለድና ሞት በምርጫ ነው?

ተሻግሮ ከበር ወዲያ ምን እንደሚገጥም አይታወቅም። በግራ ወይስ በቀኝ በር መግባት ይሻላል? በመስታወቱ ወይስ በብረቱ? በድፍኑ ወይስ በሚያሳየው? ማመንታት አለ። ባወጣው ያውጣው ብሎ የሚገባበት አለ። ምርጫው ሐዘን ሊያስከትል ይችላል፤ ደስታና ሰላም ሊያመጣ ይችላል።

አፉን ከፍቶ የሚጠብቅ በር አለ። ተዘግቶ ከመቆየት ብዛት ሸረሪት ያደራበት አለ። የሚገባበት አጥቶ የሚያዛጋ፣ መታጠፊያው የዛገ፣ ሲከፈት ቅር ቀረረረርር የሚል አለ። ተዘግቶ የማይገጥም በር አለ። በግድ የሚዘጋ፣ ቂም እንደ ያዘ ሰው ነክሦ ተደብድቦ በግድ የሚከፈት አለ። ተዘግቶ የተከፈተ ያህል አይከልል ደጅ የሆነ በር አለ። ከማዕዘኑ የተናጋ የተንጋደደ በር አለ። ሲዘጉት መልሶ መልሶ የሚከፈት፣ እንደ ችኮ ልጅ እልኽ አስጨራሽ በር አለ።
በተከፈተው ዘው ብሎ መግባት። ወይም የተዘጋውን ማንኳኳት፤ እስኪከፈት መጠበቅ። ወይም አለመጠበቅ፤ ጥሎ መሄድ። ተዘግቶ ከበስተኋላው ምን እንዳለ አያስታውቅ።
ያገኘውን በር ከፍቶ ለመግባት የሚደፍር ሰው አለ። ገብቶ በዚያው ቀረ፤ አልተመለሰም፤ በሩ በላው? መግባት የማይደፍር አለ። ስላልደፈረ፣ ምን ይጠብቀው እንደነበረ ስላላወቀ፣ እንደ ተፀፀተ ይኖራል። ምነው በገባሁ ኖሮ ይላል።

ለወዳጆቹ:- አንድ ጊዜ የተከፈተ በር አጋጥሞኝ፣ ልግባ? ልተው? ብዬ አመነታሁ። ከውስጥ የሚከፍትልኝ አይኖር ይሆን አልኩ። ኋላ ስሰማ በሩ ክፍቱን ነበር አሉኝ! የያዝኩት ቊልፍ ይከፍተው ነበር አሉኝ። እኔ ግን በሩን ከፍቼ አፋፍ ላይ ቢያወጣኝስ ብዬ ፈርቼ ተውኩት!

በተከፈተው በር አንገቴን አስገብቼ ምንም ስላላየሁ ወዲያው ተመለስኩ የሚል ደግሞ አለ፤ ለካንስ ከገባሁ በኋላ አንድ እርምጃ ወደ ቀኜ ብታጠፍ ኖሮ ወደ ትልቁ አዳራሽ የሚያስገባ ሌላ የውስጥ በር ነበር። ደርሼ ለጥቂት! ወየሁ! ምነው በገባሁ ኖሮ! ያሳለፍኩትን መከራ አላየው ነበር ይሆን?

አንዳንድ የተዘጋ በር:- ከውጭ ለቆመ “አትገባም”፤ ከውስጥ ለቆመ “አትወጣም፣ ለደህንነትህ ሲባል መዘጋቱ ይበጃል” ይለዋል።

በር ካለ፣ ከውስጥ ሰው አለ ማለት ነው? ከውስጥ ሰው ካለ፣ ከውጭ ለመግባት የሚጠብቅ ሰው መኖሩ እንዴት ይታወቃል? ከውጭ ይሁን ከውስጥ የቆመው ሰው አሳቡ በጎ ይሁን ክፉ በምን ይታወቃል? ለሚያንኳኳ ለመክፈት ወይም ላለመክፈት እንዴት መወሰን ይቻላል? የሰላም ማንኳኳት ያስታውቃል? የሰላም ማንኳኳት ከጣዕር ማንኳኳት በምን ይለያል? ማለዳ ማንኳኳት፣ እኲለ ሌት ከማንኳኳት በምን ይለያል?

ሲንኳኳ ሰምቼ ምነው በከፈትኩ ኖሮ ይላል። ለራሱና ለወዳጆቹ፦ አንድ ጊዜ ደጅ ተንኳኲቶ፣ ልክፈት? አልክፈት? ብዬ ሳመነታ እንቅልፍ ይዞኝ ጭልጥ። ጧት ስነቃ ማታ መንኳኳቱ ትዝም አላለኝ። ተንኳኲቶ እንደነበረ ያስታውስኩት ውሎ አድሮ በሁለተኛው ቀን፣ ፖሊስ በሩን ሰብሮ ገባ የሚል ዜና ስሰማ ነው።

ሲንኳኳ ሰምቼ ጆሮዬ ነው አልኩ፤ ሲደግመው ጆሮዬ ነው? ወይስ በዚህ ሰዓት ማ ያንኳኳል? አልኩ። ሲደግመው፣ ከደጅ ሰው ሳይኖር አይቀርም አልኩ። የምሩን ከሆነ ትንሽ ልጠብቅና ልይ አልኩ። ጠበቅሁ።ጠብቅሁ። ጠበቅሁ። ጥርሴ ባይኖር ልቤ ባፌ ሊወጣ ትንሽ ቀርቶት ነበር። ሳንባዬ በአየር ተወጥሯል። እንደ ገና የተንኳኳ መሰለኝ፤ ጆሮዬ ነው? ወይስ እውነት ተንኳኲቶ ነው? አላስችል ሲለኝ ብድግ ብዬ ተነሳሁና ከፈትኩ። ስከፍት ከደጅ ማንም የለም። ጆሮዬ ነው ወይስ ስዘገይ ትቶ ሄዶ ነው? አልኩ። እስከ ዛሬ መልስ አላገኘሁለትም።

አራት በር ፊቴ ተደቅኗል። በቢጫው ወይስ በቀዩ ወይስ በሰማያዊው ልግባ? አራተኛው በር ደጅ ይመስላል፤ ክፍት ነው ወይስ ዝግ? ልግባበት ወይስ ይቅር?

©2020 by Mitiku Adisu| ጥር 28፣ 2012 ዓ.ም.

Share this post