እስራኤል እና ዩናይትድ ስቴትስ በኢራን ላይ እንደገና ጥቃትን ለመጀመር እየተዘጋጁ ነው

እስራኤል እና ዩናይትድ ስቴትስ በኢራን ላይ እንደገና ጥቃትን ለመጀመር እየተዘጋጁ ነው

እስራኤል እና ዩናይትድ ስቴትስ በኢራን ላይ እንደገና ጥቃትን ለመጀመር ከፍተኛ ዝግጅቶችን እያካሄዱ እንደሆነ ኒውዮርክ ታይምስ ዘገበ። አዲሱ ጥቃት ከዚህ በፊት ከተፈፀሙት ሁሉ የጠነከረ ሊሆን እንደሚችል ሁለት ባለስልጣኖችን በመጥቀስ ጋዜጣው ዘግቧል።ጋዜጣው የጠቀሳቸው የአሜሪካ ኃላፊዎች እንደሚሉት፣ በኢራን ላይ እንደገና ሊደረጉ ከታሰቡት የተቀናጁ ጥቃቶች መካከል ከባድ የቦምብ ጥቃቶችን በወታደራዊና መሠረተ ልማት ኢላማዎች ላይ ማካሄድ፣ በሰሜናዊ ባሕረ ሰላጤ በኻርግ ደሴት የሚገኘውን እና ኢራን ነዳጅ ለውጭ ገበያ የምትልክበት ቁልፍ መተላለፊያን መቆጣጠር፣ እና ከምድር በታች የሚገኙ የኒውክሌር ኃይል ማበልጸጊያ ቁሳቁስ ለማውጣት ኮማንዶዎችን ወደ ወደ ቦታው መላክን ያካትታሉ።

ከኢራን የበለጸገውን ዩራኒየም ማውጣት ከባድና አስቸጋሪ መሆኑን የዘገበው ጋዜጣው በሂደቱ ብዙ ሰዎች ሊጎዱ የሚችሉበት አደጋ ሊያጋጥም እንደሚችል አስታውቋል።ኦፕሬሽኑን ለማካሄድ የደህንነት ቀጠና ለመፍጠር እንዲሁም ከኢራን የምድር ጦር ኃይሎች ጋር ሊዋጉ የሚችሉ በሺዎች የሚቆጠሩ የምድር ጦር ኃይሎች እንደሚያስፈልግ ጋዜጣው ጠቅሷል።
የመከላከያ ሚኒስትሩ ፒት ሄግሴት ማክሰኞ ለሕግ አውጭዎች እንደተናገሩት፣ አሜሪካ “አስፈላጊ ከሆነ በበለጠ ጥንካሬ እና ከፍ ባለ ኃይል ኢራንን ትመታለች” በማለት ተናግረዋል።

ካለፈው ወር ጀምሮ በአሜሪካና በኢራን መካከል የተደረሰው የተኩስ አቁም ስምምነት የሰላም ውይይቶቹን ለማካሄድ ያስችላል ተብሎ የነበረ ቢሆንም ይህ ነው የሚባል ውጤት ሳይገኝ ቀርቷል። በሁለቱ አገራት መካከል የሚደረገውን ንግግር ፓኪስታን እያሸማገለች ትገኛለች። ነገር ግን ሁለቱም ወገኖች በሀሳብ ተራርቀው የታዩ ሲሆን፤ አገራቱ ጦርነቱን ለማስቆም የቀረቡትን ሀሳቦች ውድቅ አድርገዋል

የአሜሪካው ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ ዓርብ ለፎክስ ኒውዝ እንደተናገሩት፣ ኢራን ከዚህ በፊት ተስማምታው የነበሩ በርካታ ስምምነቶችን ለመቀበል ፈቃደኛ አልሆነችም። “ስምምነት ባደረግን ጊዜ፣ በሚቀጥለው ቀን ‘ምንም የምናውቀው ነገር’ በማለት ይክዳሉ” ሲሉ ትራምፕ ተናግረዋል።

Share this post

Post Comment